Thursday, August 03, 2006

Message from Dawit Kebede

ይድረስ በጋዜጠኝነት ሙያ ለተሰማራችሁ ወንድሞቼ… ኦገስት 4 ቀን፣ 2006 ዓ .ም ይህንን ደብዳቤ ለመጻፍ የተገደድነው ሰሞኑን በአንዳንድ ድረ ገጾች ላይ የሚወጡትን አሉባልታዎች ከተመለከትን በኋላ ነው። በተለይም እነዚህ አሉባልታዎች በቀጥታ በቅንጅቱ አመራር ላይ የተሰነዘሩ ከመሆን አልፈው፤ የህዝቡንም የትግል መንፈስ የሚዳክሙ በመሆናቸው እና ህዝብም የማወቅ መብት ስላለው ሃቁን ከዚህ በታች አናቀርባለን። ከዚሁ ጋር በተያያዘ የኢትዮጵያ ጋዜጠኞች የተሳሳተውን ፈለግ እንዳይከተሉ ይህ ማስታወሻ የራሱን ሚና ይጫወታል፤ ከሙያዊ ግድፈትም ያድናቸዋል የሚል እምነት አለን። የዚህ ማስታወሻ ሌላኛው አላማ የኢትዮጵያ ህዝብ እውነቱን አውቆ መንገዱን ከቅንጅትም ሆነ ከሚያምነው የፖለቲካ ድርጅት ጋር እንዲያደርግ ዳግም ጥሪ ለማድረግ ጭምር ነው። በሌላም በኩል ታሪካቸውን በወርቅ ቀለም ያስጻፉና በስደት ላይ የሚገኙ የኢትዮጵያ ነጻ ፕሬስ ጋዜጠኞች ሌሎች ድረ -ወጦችን ተከትለው ስማቸውንና ስማችንን በቁሻሻ እንዳይለውሱት ነው። እኛ ሌሎችን አይደለንም። የራሳችን የሆነ ህግና ስርአት ያለን መሆናችንን ምንግዜም እናስታውስ። ለውሳኔ ቸኩለን የብእራችንን ጦር በቅንጅት ወይም በሌላ ድርጅት ላይ ከማዞራችን በፊት ቃል የገባንለትን የኢነጋማ ፕሮፌሽናል ጋዜጠኞች መመሪያ እናስታውስ። ይህ መመሪያ ደግሞ ለኢነጋማ አባላት ብቻ ሳይሆን በውጭ ለሚገኙ ሌሎች ጋዜጠኞችም ጠቃሚነቱ አሌ የሚባል ባለመሆኑ ሌሎች ጋዜጠኞችም በተግባር እንዲያውሉት ያስፈልጋል። በተለይም በቁጥር 1 እና 4 ላይ የተመለከቱትን ህጎች መጠበቅ አስፈላጊነቱ አያጠያይቅም። ውድ ጋዜጠኞች… እንደምታውቁት ኢትዮጵያ ውስጥ በነበርንበት ወቅት “ሃሳብን በነጻ ለመግለጽ መብት” ታገልን እንጂ፤ ለአሉባልታና ለሃሜት አልታሰርንም፤ ዛሬም ቢሆን በዚህ አንታማም። አገር ቤት በነበርንበት ወቅት የወያኔ ባለስልጣናት የመረጃ ምንጮቻችንን በመዝጋታቸው፤ ትግላችንን አራዘመው። …ዛሬም ቢሆን መረጃ አግኝተን ሃሳባችንን በነጻ ለመግለጽ ምንግዜም አብረን እንቆማለን። ይህ ሃቅ እንደተጠበቀ ሆኖ፤ አሁን የምንተቸው ቅንጅት ግን እንደ ወያኔ በሩን ያልዘጋብን መሆኑን መዘንጋት የለብንም። ይህንን በር እናንኳኳ፤ ይከፈትልናል። እንጠይቅ… ይመለስልናል። ይህንን ሞክረን ካልተሳካ እንጂ የፕሬስ ነጻነት ትግላችን መቀጠል ያለበት… እንዲያው በአሉባልታ ከሌሎች ጋር በመሆን፤ ጭብጥ በሌለው ወሬ አሳሳች ከበሮ መደለቁ አስፈላጊነቱ አይታየንም። እርግጥ ነው፤ በአሁኑ ወቅት የተፈጠረው የመረጃ ክፍተት ወደ አላስፈላጊ ውዝግብ ውስጥ እንደከተታችሁ እንገነዘባለን። በመሆኑም “ህዝብ የማወቅ መብት አለው” የሚለው መመሪያችን እንደተጠበቀ ሆኖ፤ የድርጅቶችንም የውስጥ ነጻነት ባልተሸራረፈ መልኩ ልናከብር ይገባናል። ስለሆነም ጋዜጠኞችና ሌላውም ህብረተሰብ ማወቅ የሚገባውን ሃቅ ማሳወቅ ይገባቸዋል። ከዚህ ቀጥሎ ያለውም ባለ 24 ነጥብ ማስታወሻ እንደመነሻ ሆኖ ሊያገለግለን ይችላል። ከዚህም ሃቅ በመነሳት እውነቱን ለህዝባችን ማሳወቅ ወቅቱ የሚጠይቀው ሙያዊ ግዴታችን ነው። 1- በመላው አለም የሚገኙ የድጋፍ ሰጪዎች ታሪክ በባህር ማዶ የነበሩ የፖለቲካ ድርጅቶች በቀዳሚነት የሚያደራጁት የፖለቲካ ፕሮግራማቸውን የተቀበሉ ግለሰቦችንና ቡድኖችን ነበር። ሆኖም ትግሉ በኢትዮጵያ ውስጥ መሆኑን ግንዛቤ ላይ ሲደረስ፤ በውጭ የተደራጁ የፖለቲካ ድርጅቶች እየተዳከሙ፤ በሌላ በኩል ደግሞ የአገር ቤቱ ትግል እየተፋፋመ መጣ። በዚህን ወቅት የውጭው ሃይል ድጋፉን በፖለቲካ መስመር ብቻ ሳይሆን፤ በፋይናንስ እርዳታና በዲፕሎማሲያዊ ግንኙነት በኩል ማጠናከሩ አስፈላጊነቱ ታመነበት። በመሆኑም በአገር ቤት ያሉትን ፓርቲዎች የሚደግፉ ቡድኖች ተበራከቱ። ትግሉም የፖለቲካ ድርጅት አባል በመሆን ብቻ ሳይሆን የድጋፍ ድርጅት አባላትም በባህር ማዶ የሰላማዊ ትግሉ አንድ አካል መሆን ጀመሩ። ከዚያን ጊዜ ጀምሮ በመላው አለም የሚገኙ የድጋፍ ሰጪ አካላትም እየተበራከቱ መጡ። 2- የሰሜን አሜሪካ የድጋፍ ሰጪ አካላት ታሪክ (ከምርጫው በፊት ) የሰሜን አሜሪካ የድጋፍ ሰጪ አካላት ታሪክ ከሌሎች ድጋፍ ሰጪዎች የተለየ ታሪክ ባይኖረውም፤ ማእከላዊነትን የጠበቀ፤ በህግ የሚመራና ብዙዎችን የሚያሳትፍ ሆኖ የተመሰረተ ነው። በተለይም ቅንጅትን ከመሰረቱት አራት ፓርቲዎች መካከል ሁለቱ ጠንካራ የድጋፍ ሰጪ አካላት የነበሯቸው ሲሆኑ፤ ቅንጅቱ ከመዋሃዱ በፊት የነዚህ ሁለት ፓርቲዎች ድጋፍ ሰጪዎች በየራሳቸው ፓርቲዎቻቸውን እስከምርጫው ሰሞን መደገፋቸውን ቀጠሉ፤ በወቅቱ በጋራ ከመስራት አልፈው አልተዋሃዱም ነበር። 2005----- 3- የፖለቲካ ድርጅት ቀጥተኛ ተወካዮች ቅንጅቱ ወደ ምርጫው ሊገባ ሰሞን፤ የቅንጅቱ ፖለቲካ ድርጅቶች በባህር ማዶ የሚገኙ ተወካዮቻቸውን አሳወቁ። በዚህም መሰረት ከኢዴሊ በስተቀር ሶስቱም በተወካዮቻቸው አማካኝነት በልዩ ልዩ የአሜሪካ ክፍለ ግዛቶች ከህዝቡ ጋር ስብሰባዎችን ማድረግ ጀመሩ። 4- የድጋፍ ድርጅቶችን የማጠናከር ተግባር የቅንጅት ከፍተኛ አመራሮች አሜሪካ በመጡበት ወቅት፤ የልዩ ልዩ የድጋፍ ሰጪ አካላት ተዋህደው ስራ ባለመጀመራቸው በዋሺንግተን ዲሲ የሚገኘው አመራር ባስቸኳይ ድጋፍ ሰጪዎችን እንዲያንቀሳቅስ ታዘዘ ቀረበ። ከሶስቱ ሰዎች በተጨማሪ ሌሎች ሰዎች ተጨምረው ስራ እንዲጀመርም ሃሳብ ቀረበ። 5- ተጨማሪ አመራር አባላትን ማካተት አዲስ አበባ የሚገኘው የቅንጅቱ የበላይ አካላት ባሳሰቡት መሰረት በሶስቱ ሰዎች ላይ ሌሎች ሰባት ሰዎች ተጨምረው አስር ሰዎች ያሉበት የአመራር አካል ተፈጠረ። ከዚህ በኋላ መመሪያዎችን ለድጋፍ ድርጅቶች በማውረድ፤ በየቦታው የሚገኙ የልዩ ልዩ ፓርቲዎች ድጋፍ ሰጪ ድርጅቶች እንዲዋሃዱና ስራ እንዲጀምሩ ተባለ፤ ይህም ያለ ብዙ ችግር ተፈጻሚ ሆነ። 2006 ---- 6- የሰሜን አሜሪካ የቅንጅት አባላት ጠቅላላ ጉባዔ የመጀመሪያ ጉባዔ ከውህደቱ በኋላ በወርሃ ጃኑዋሪ የተዋሃዱትና አዲስ የተመሰረቱት የቅንጅት የድጋፍ ሰጪ ድርጅት አባላት ዋሺንግተን ላይ ለመጀመሪያ ጊዜ ጠቅላላ ጉባዔ አደረጉ፤ በሁለት ቀን ተከታታይ ስብሰባቸውም የስራ እቅዳቸውን አወጡ። ቀጣዩ ጉባዔ በዚያው በዋሺንግተን ዲሲ፤ በግንቦት ወር እንዲከናወን ተወሰነ። 7- የሰሜን አሜሪካ የቅንጅት አባላት ጠቅላላ ጉባዔ ሁለተኛ ጉባዔ 2ኛው ጠቅላላ ጉባዔ በግንቦት ወር 2006 ዓ .ም ተከናወነ። በዚህ ጉባዔ ላይ አመራሩ የስራ ሪፖርቱን ለአባላት አቀረበ። የአቃቤ ንዋይና የፋይናንስ ኦዲተር ሪፖርት ተደመጠ። በዚህ ጉባዔ ላይ ቀደም ሲል የነበሩት አስር አመራሮች ባሉበት ሁኔታ እንዲቀጥሉ ተወሰነ፤ ሌሎች አምስት ሰዎችም ተመረጡ። በዚህ ስብሰባ ላይ የተነሳው አዲስ ነገር ቢኖር በቃሊቲ የሚገኙ የቅንጅቱ መሪዎች ያለውን የፖለቲካ ክፍተት ለመሙላት ስድስት ሰዎች የተሰየሙ መሆናቸው ነበር። ይህ ጉዳይ ለመጀመሪያ ጊዜ ሲሰማ ግራ መጋባት ቢፈጥርም፤ ሃላፊነቱ ለአመራሩ እንዲሰጥና ስምምነት ላይ እንዲደረስ ተወሰነ። በመጨረሻም ቀጣዩ የካውንስል ወይም የምክር ቤት አባላት ስብሰባ በጁላይ ወር፣ ሎስ አንጀለስ ላይ እንዲደረግ ተወሰነ። 3ኛው ጠቅላላ ጉባዔም ከ 6 ወራት በኋላ ቦስተን ላይ እንዲሆን ስምምነት ላይ ተደረሰ። 8- ኦዲተርና የኦዲት ሪፖርት የሰሜን አሜሪካ የቅንጅት የሂሳብ መርማሪ ወይም ኦዲተር ለመጀመሪያ ጊዜ የተዋወቀው በ 2ኛው ጉባዔ ላይ ነው። ኦዲተሩ ሪፖርቱን ከማስደመጡ በፊት ለሰሜን አሜሪካ ጠቅላላ ጉባዔ እንደገለጸው፤ “ባለፉት 30 አመታት አንድም የፖለቲካ ድርጅት በውጭ ኦዲተር ሂሳቡን አስመርምሮ አያውቅም። እንኳንስ ማስመርመር ቀርቶ ለማስመርመርም ፈቃደኞች አይደሉም። የሰሜን አሜሪካ ቅንጅት ግን ይህንን በማድረጉ ሊመሰገን ይገባዋል።” በማለት ያላቸውን አድናቆት ገልፀዋል። ሆኖም ለጥንቃቄ ሲባል፤ የኦዲት ሪፖርታቸውን በዝርዝር ሳይሆን በደፈናው ገልጸዋል። ዝርዝሩን ከስራ አስፈጻሚው አካል ጋር ተወያይተውበታል። እኚህ የውጭ ኦዲተር ገንዘብ ሳይከፈላቸው በነጻ ወደ ድርጅቱ መጥተው ይህንን በማድረጋቸው በወቅቱ ሁሉም ደስታውን ገልጾላቸዋል። 9- ከስራ መልቀቅ ከላይ እንደተገለጸው ኦዲተሩ በራሳቸው ፈቃድ፤ ወደ ሰሜን አሜሪካ ቅንጅት በመምጣት አብረው በመስራታቸው ሁሉም እጁን ዘርግቶ በደስታ ነበር የተቀበላቸው። ነገር ግን በፈቃደኝነት ለኦዲቲንግ እንደመጡት ሁሉ በፈቃደኝነት ስራውን በሁለት መስመር ማሳሰቢያ ሲለቁ፤ በግድ እንዲቆዩ ማስገደድ አስቸጋሪ ነበር። በተለይም በገንዘብ ያልተቀጠረንና በህዝብ ያልተመረጠን ሰው ማስገደድ የሚቻል እንዳልሆነ ማንኛውም ሰው የሚገነዘበው ይመስለናል። ሰለሆነም ግለሰቡን በአክብሮት አነጋግሮና በፍቅር ሸኝቶ ሌላ ሰው በመተካት ስራው ወደፊት እንዲሄድ ነው መደረግ ያለበት። 10- የፋይናንስ ወጪዎች የሰሜን አሜሪካ የቅንጅት ወጪዎች የታወቁ ናቸው። እነዚህ በውል የምናውቃቸው ወጪዎች፤ ኢትዮጵያ ውስጥ የታሰሩትን የቅንጅት መሪዎች ቤተሰብ መርዳት፣ የቅንጅት መሪዎችን ለማስፈታት በየወሩ እስከ 40 ሺህ ዶላር የሚከፈል የሎቢስቶች ወጪ፣ የቢሮ ስራ ማስኬጃና የቢሮ ሰራተኞች ወጪዎች የሚጠቀሱ ናቸው። ይህንን በማድረጋቸው የቅንጅቱ ደጋፊዎችና አመራር አባላት ሊመሰገኑ ይገባቸዋል ወይስ ሊወቀስ ? መልሱን የቅንጅቱን ስም በማጥፋት ተግባር ላይ ለተሰማሩት እንተወዋለን። 11- የገንዘብ ብክነት የቅንጅት ድጋፍ ሰጪዎችም ሆነ የአመራር አባላት ከራሳቸው ኪስ ገንዘብ እያወጡ ድርጅቱን ከመደገፍ አልፈው አንድም ጊዜ ገንዘብ ያባከኑበት ጊዜ የለም። ከዚህ ውጪ ግን የቅንጅት ድጋፍ ሰጪ አባላት ሳይሆኑ በራሳቸው ጊዜ ኮሚቴ አቋቁመው፤ በራሳቸው መንገድ ገንዘብ የሰበሰቡ ካሉ ለድርጅቱ ሪፖርት ቢደረግና ቢጣራ እንጂ የሚሻለው፤ በደፈናው የድርጅቱን ስም ማጉደፍ ለህሊና የሚከብድ ተግባር ነው። 12- ቅንጅትና የትብብር ለነጻነትና ዲሞክራሲ አመሰራረት ሁለተኛው የሰሜን አሜሪካ ቅንጅት ጠቅላላ ጉባዔ እንደተጠናቀቀ በሚቀጥለው ቀን ሶስት ሰዎች የሚገኙበትና በአመራሩ የፖለቲካ አባላት የሚመራ የልኡካን ቡድን ወደ አውሮፓ አመራ። የዚህ የልኡካን ቡድን አላማ ቀደም ሲል ተጀምሮ የነበረውን የትብብር ሰነድ ላይ ለመነጋገር ነበር። ከሶስት ቀኑ የዩትሬክት፣ ኔዘርላንድ ስብሰባ ሲጠናቀቅ እና የመግባቢያ ሰነዱ ላይ ከተፈረመ በኋላ ዜናው ለህዝብ ይፋ ሆነ። 13- የመጀመሪያው የሰሜን አሜሪካ አመራሮች ስብሰባ ከ 2ኛው ጉባዔ በኋላ፤ የመጀመሪያው የሰሜን አሜሪካ አመራሮች ስብሰባ አደረጉ። በዚህ ስብሰባ ላይ ከቃሊቲ የተላከው ደብዳቤ እና የአለም አቀፉ አመራር ኮሚቴ አመሰራረትን በተመለከተ ሰፊ ውይይት ተደረገ። በዚህም መሰረት ከቃሊቲ የመጣው ደብዳቤ ትክክለኛነቱ ታመነበት። ከዚሁ ጋር ተያይዞም የቅንጅት አለም አቀፍ የፖለቲካ አመራር ኮሚቴ፤ ከአዲስ አበባ በተላለፈው መመሪያ ተጨማሪ 6 ሰዎችን አካተው ስራቸውን እንዲጀምሩ ስምምነት ላይ ተደረሰ። 14- የቅንጅት አለም አቀፍ የፖለቲካ አመራር ኮሚቴ መቋቋም የቅንጅት አለም አቀፍ ኮሚቴ የተቋቋመው ከላይ በተገለጸው መሰረት ሲሆን፤ ተጨማሪ 6 ሰዎችን በማካተት ስራውን ጀመረ። የመጀመሪያውንም ስብሰባ በጁን 20ዎቹ መጀመሪያ ላይ አደረገ። 12 ሰዎች ያሉበት የፖለቲካ አመራር አካላት ያሉበት ኮሚቴ ለሶስት ቀናት ባደረገው ስብሰባ፤ የስራ እቅዱን ከመንደፉም በተጨማሪ፤ ከአዲስ አበባ በመጣው መመሪያ መሰረት መሪዎቹንና የዘርፍ ሃላፊዎችን መርጧል። በህግና ደንቡም ላይ ተነጋግሯል። ከምንም በላይ ደግሞ የፖለቲካ ውሳኔ የሚያስፈልጋቸውን --- እንደ “ትብብር ለነጻነትና ዲሞክራሲ”ን በተመለክተ በሃላፊነት እንዲመራ ተደርጓል። ስለትብብሩም በተከታታይ መግለጫ ተሰጥቷል። 15- የሰሜን አሜሪካ የቅንጅት ምክር ቤት (ካውንስል ) የመጀመሪያው የቅንጅት ድጋፍ ሰጪ አካላት የካውንስል ስብሰባ ጁላይ 5 ቀን፣ 2006 ዓ .ም ሎስ አንጀለስ ላይ ተደረገ። በሎስ አንጀለሱ የሰሜን አሜሪካ የቅንጅት ምክር ቤት አባላት ስብሰባ ላይ የአለም አቀፉ ኮሚቴ አባላትም ተገኙ። የካውንስሉ አባላት አለም አቀፉን አካል መቀበላቸውን ከገለጹ በኋል መሰረታዊ ጥያቄ አነሱ። ይኸውም፤ “የቅንጅት አለም አቀፍ ኮሚቴና የሰሜን አሜሪካ የድጋፍ ድርጅት አባላት ወደፊት ሊኖራቸው የሚችለው የስራ ግንኙነት ምን ይሆናል ?” የሚለው በአበይትነት ይጠቀሳል። በዚህ ጉዳይ በርካታ ውይይት ከተደረገ በኋላ፤ “የቅንጅት አለም አቀፍ ኮሚቴ በአንድ ወር ጊዜ ውስጥ ይህንን ለካውንስሉ እንዲያሳውቅ” የሚል ውሳኔ ተሰጠ። ይህም ቀደም ብሎ አመራሩ ከሰጠው ውሳኔ ጋር ተመሳሳይ የሆነ ውሳኔ ነበር። 16- የሃሳብ ልዩነቶች ከላይ የተገለጸውን የሰሜን አሜሪካ የካውንስል ውሳኔ መሰረት በማድረግ አለም አቀፉ የቅንጅት አመራር፤ ከመማክርት ምክር ቤት አባላት ጋር በመሆን ስራውን በማከናወን ላይ ነው። በዚህና በሌሎች ጉዳዮች ላይ አባላት በዲሞክራሲያዊ መንገድ በመወያየት ላይ ናቸው። አንደኛው ወገን “አለም አቀፉ ኮሚቴ በቀጥታ በድጋፍ ሰጪዎች ጉዳይ ሊገባ ይገባዋል” ሲል፤ ሌላኛው ወገን ደግሞ፤ “አለም አቀፉ ኮሚቴ መመሪያውን ለሰሜን አሜሪካ ወይም ለሌላው አህጉር አመራር ያስተላልፋል። የየአህጉሩ አመራሮችም መመሪያውን ያስፈጽማሉ”… የሚል ነው። ይህ ነው በመሰረታዊነት ቅንጅቱን እያነጋገረ ያለው። ይህ ደግሞ አንድ ጤነኛ ፓርቲ ውስጥ ሊኖር የሚገባና የሚበረታታ ነው። ሃሳቦች ተንሸራሽረው በድምጽ ብልጫ ከተወሰኑ በኋላ ሁሉም ለብዙሃኑ ድምጽ ተገዢ ሆኖ ስራውን ይቀጥላል። ይህ የሚያኮራ እንጂ የሚያለያይ ጉዳይ ተደርጎ መወሰድ የለበትም። 17- የሃሳብ አንድነት የሰሜን አሜሪካ ሆነ የአለም አቀፉ አመራር ወይም የድጋፍ ሰጪ አባላት ኢትዮጵያ ውስጥ የታሰሩትን መሪዎቻቸውን ለማስፈታት በሚደረገው ጥረት ተሳታፊዎች ናቸው። የቅንጅት መሪዎች ከመታሰራቸው በፊት አቅርበዋቸው የነበሩትን 8 ነጥቦች አሁንም ሆነ ወደፊት በአንድነት እያራመዱት ነው። በትብብር ለነጻነትና ዲሞክራሲ ሁሉም ድጋፉን በመስጠት ላይ ይገኛል። ቀድሞውኑም የተነሱለትንና የኢትዮጵያ ህዝብ በአንድነቱ እንዲገፋና የዲሞክራሲ ተጠቃሚ እንዲሆን የሚደረገው ትግል በመቀጠሉ ላይ፤ ወይም አምባ ገነኑን የወያኔ አስተዳደር ገርስሶ ለመጣል በሚደረገው ሰላማዊ ትግል ውስጥ ተሳታፊዎች ናቸው። 18- የቅንጅቱ ድረ -ገፅ አለም አቀፉ የቅንጅት አመራር የራሱ የሆነ ድረ ገፅ እስከሞኖረው ድረስ አሁን ያለውን የ“ቅንጅት” ድረ ገፅ ይጠቀማል፤ እየተጠቀመም ነው። በተደጋጋሚ የሚወጡ መግለጫዎችም በዚሁ ድረ ገጽ ላይ ለህትመት ቀርበዋል። ሆኖም የዚህ ድረ ገፅ ሁኔታን የሚወስነው፤ የአለም አቀፉ ኮሚቴ ከሰሜን አሜሪካው አመራር ጋር የሚኖረው ግንኙነት ይሆናል። ይህም በቀጣዩ ስብሰባ ላይ የሚታይ ሊሆን ይሆን ይሆናል። 19- ቀጣዩ የቅንጅት ድጋፍ ሰጪ አካላት ካውንስል ስብሰባ ከላይ የተገለጹትንና ሌሎችንም ጉዳዮች ለመወሰን በኦገስት ወር መጨረሻ አካባቢ ምክር ቤቱ ይሰበሰባል። 20- ቀጣዩ የቅንጅት ድጋፍ ሰጪ አካላት ጠቅላላ ጉባዔ ቀደም ተብሎ በተያዘው እቅድ መሰረትም ቀጣዩ የድጋፍ ሰጪ አካላት ጠቅላላ ጉባዔ በወርሃ ኖቬምበር፣ 2006 ዓ .ም ቦስተን ላይ ይሰበሰባል። 21- ቅንጅት ወዴት እያመራ ነው ? በውጭ አገር የሚገኘው የቅንጅት አለም አቀፍ የፖለቲካ አመራር ወይም የድጋፍ ሰጪ አካላት ስራቸውን አላቋረጡም። የአመራር አካላት ቢያንስ በሳምንት አንድ ጊዜ ስብሰባ ያደርጋሉ። የድጋፍ ሰጪ ኮሚቴ አባላትም ሆኑ አመራሮች ጊዜያቸውንና ገንዘባቸውን በማውጣት በኢትዮጵያ የሚደረገውን ሰላማዊ ትግል በመደገፍ ላይ ናቸው። ለስብሰባ ከአንዱ ስፍራ ወደ ሌላው ሲሄዱ በራሳቸው ወጪ መሆኑንም መዘንጋት አይገባም። ይህ እራሱን ለቅንጅት መርህ ተገዢ ያደረገ ሃይል፤ ቅንጅቱን በመደገፍ ወደፊት ያመራል እንጂ ከቶውኑም በአሉባልታ ተደነቃቅፎ አይቀርም። ይህ በህዝቦች የደም መስዋእትነት የተገኘ ድርጅት በባህር ማዶ ከሚያደርገው የዲፕሎማሲ ትግል በተጨማሪ፤ ሰላማዊ ትግሉ በአገር ቤት እንዲፋፋም ጥረት በማድረግ ላይ ነው። ሰላማዊው ትግልም የቅንጅቱን መሪዎች ከእስር ከማስፈታት አልፎ፤ ለኢትዮጵያ ያለውን ራዕይ እንደጠበቀ ታሪካዊ የትግል ጉዞውን ይቀጥላል። 22- ግልጽነት ቅንጅት በግልጽ ከህዝብ ጋር የሚሰራ ድርጅት ነው። ለዚህ ማንም ጥርጣሬ ሊኖረው አይገባም። ሆኖም ግን መጠን ያለፈና ድርጅቱን አደጋ ላይ የሚጥሉ ነገሮችን የሚመቻችበት ምንም ምክንያት አይኖርም። በተለይም የፖለቲካው ስራ በህቡዕ እና በግልጽ እየተሰራ ነው። ዛሬ የምናደርገውን እያንዳንዱን የፖለቲካ ውሳኔ የወያኔ አስተዳደር መልሶ የቅንጅት መሪዎችን ለመክሰስና እንደመረጃ ለማቅረብ በሚሯሯጥበት ወቅት መረጃ አቀባይ ካልሆናችሁ ብሎ ሙግት መግጠሙ በራሱ ትክክል አይሆንም። ይህም እንደጥንካሬ እንጂ እንደደካማነት ሊታይ የሚገባው አይደለም። ከዚህ በተጨማሪም የውስጥ አሰራሮችና የፋይናንስ አወጣጦችን በተመለከተ አቃቤ ንዋይና ኦዲተር ሪፖርቱን ለስሜን ሜሪካ የድጋፍ ሰጪዎች ምክር ቤት ያቀርባል እንጂ፤ ለመላው አለም ህዝብ ሪፖርት እንዲያደርግ መጠየቅ የፖለቲካ ብስለትን አያሳይም። 23- አመራር በተደጋጋሚ በድረ ገጾች ላይ የሚነሳ ጉዳይ አለ። አመራሩ ደካማ እንደሆነ ተደርጎ የሚገለጽ ነገር አለ። ይህ አይነቱ ሂስ ጤናማ ሊሆን የሚችለው በትክክለኛ መንገድ ድክመቱን እና መፍትሄውን ጭምር በማቅረብ እንጂ በደፈናው በመተቸት አይደለም። በየትኛውም ወገን ያለ አመራር በድምጽ ለተወሰኑ ሃሳቦች እራሱን ተገዢ አድርጎ፤ በዲሞክራሲያዊ መንገድ እየሰራ በሚገኝበት ባሁኑ ወቅት በደፈናው ትችትና አሉባልታ ማስተጋባት ፈጽሞ ከማንም የሚጠበቅ አይደለም። እዚህ ላይ ሳይጠቀስ የማይታለፍ ነገር አለ። የሰሜን አሜሪካም ሆነ፤ የአለም አቀፉን ቅንጅት በሊቀመንበርነት የሚመሩት ሻለቃ ዮሴፍ ናቸው። ላለፉት 30 አመታት ከትጥቅ ትግል ጀምሮ፤ አሁን ደግሞ በሰላማዊ መንገድ ለአገራቸው የሚተጉና የሚሰሩ ሰው መሆናቸው ይታወቃል። ነገሮችን በእርጋታ የመመልከትና የአስታራቂነት ባህሪያቸው በተደጋጋሚ እንዲመረጡ ያደረጋቸው ይመስላል። በርግጥም በአሁኑም ወቅት ለአገራችን የሚያስፈልጋት እርጋታን የተላበሰ፤ ከስሜታዊነት የጸዳ እና ቢያንስ አምባገነን ያልሆነ ሰው ነው። እንዲህ አይነት ሰዎች በብዛት ማግኘታችን ደግሞ ቅንጅትን የሚያኮራው ጉዳይ ይሆናል። ከዚያ ውጪ ግን አመራሩ ውስጥ ያሉ ሰዎች ጠንካራም ሆነ ደካማ ጎን ሊኖራቸው ይችላል። ጠንካራውን ይበልጥ እያበረታታን ደካማው ከስህተቱ ተምሮ ለበለጠ ስራ የሚተጋበትን መንገድ መቀየስ እንጂ የሚጠበቅብን፤ እርስ በርስ ማናቆር ከጋዜጠኛውም ሆነ ከህብረተሰቡ የሚጠበቅ አይደለም። በመሆኑም ህብረተሰቡን ከማስተማር አልፈን ሚዛናዊ የሆኑ ዘገባዎችን በማቅረብ ወቅቱ የሚጠብቅብንን አደራ ልንወጣ ይገባል። 24- ከደጋፊዎችና ከህብረተሰቡ ምን ይጠበቃል ? በውጭ አገር የሚገኙ ደጋፊዎች በፋይናንስና በዲፕሎማሲው ረገድ ከሚያደርጉት አስተዋጽኦ በተጨማሪ የሰልማዊው ትግል ባለቤቶች መሆን ይኖርባቸዋል። እንደሚታወቀው ቅንጅት የመረጠው የትግል ስልት ሰላማዊ የሆነውንና ትእግስት አስጨራሹን የትግል መስመር ነው። ይህ ትግል ደግሞ በግብታዊነት የሚመራ ሳይሆን በሰከነ አዕምሮና በሚዛናዊነት መሆኑ ለሁሉም ግልጽ ነው። ሚዛናዊ የሆነ ትግል ማድረግ የሚቻለው ደግሞ ሁሉም ወደ አንድ አስተሳሰብ ሲቃረብ እንጂ፤ በተናጥል በሚደረግ ጉዞ አይደለም። በእርግጥ የቅንጅቱን አላማ ተከትለው የሚሄዱ አባላት ይህንን የጋራ አሰራር የመከተል የሞራል ግዴታ አለባቸው። ለዚህም በተከታታይ በሚደረገው የትግል መስመር ውስጥ መሳተፍ እና በጎደለው የትግል ስፍራ እራሳቸውን ተሳታፊ ማድረግ ይጠበቅባቸዋል። ለዚህ ሰላማዊ ትግልም ትእግስትና ያላሰለሰ ተከታታይ ተሳታፊነት አስፈላጊ ነው። ጋዜጠኞችም ሆኑ ህብረተሰቡ ይህንን ሰላማዊ ትግል ለማጎልበት ያላወቁትን እንዲያውቁ ያወቁትን እንዲበረቱ ማድረግ ህዝባችን የሚጠብቀው ወቅታዊ ግዴታ ይሆናል። Source

1 comment:

Ethiopis said...

check